ብሪክስ ፍትኃዊና ወካይ የዓለም ሥርዓት ለመፍጠር ከፍተኛ ሚና ያበረክታል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
ብሪክስ ፍትኃዊና ወካይ የዓለም ሥርዓት ለመፍጠር ከፍተኛ ሚና ያበረክታል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 13/2017(ኢዜአ)፡- ብሪክስ ፍትኃዊና ወካይ የዓለም ሥርዓት ለመፍጠር ከፍተኛ ሚና እንደሚያበረክት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ተናገሩ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሩሲያ ካዛን እየተካሄደ ባለው 16ኛው የብሪክስ ጉባኤ ላይ መልዕክት አስተላልፈዋል።
በመልዕክታቸውም ኢትዮጵያ ሁሉንም ተጠቃሚ በሚያደርጉ የባለብዙ ወገን መድረኮች ላይ የምታደርገውን ተሳትፎ አጠናክራ እንደምትቀጥል ተናግረዋል።
ዓለም እየገጠማት ካለው ፈተና አንጻር ሁሉንም ተጠቃሚ የሚያደርግ ጥበብ የተሞላበት አካሄድ እንደሚያስፈልግም ነው የገለጹት።
በተለይም የታዳጊ ሀገራት ኢኮኖሚ ፍትኃዊ ባልሆነ የዓለም የፋይናንስ ሥርዓት እየተፈተነ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም ሥራ አጥነትና የዋጋ ንረትን እያስከተለ ነው ብለዋል።
ከዚህ አኳያ ብሪክስ የተሻሉ እድሎችን ይዞ መምጣቱን ነው የተናገሩት።
የዓለምን ግማሽ ያህል የሚጠጋ የሕዝብ ቁጥር የሚይዘው ብሪክስ በዓለም አቀፍ ደረጃ ፍትኃዊ ሥርዓትን በማስፈን ረገድ ሚናው የጎላ መሆኑንም አንስተዋል።
በብሪክስ ሀገራት መካከል ጠንካራና አብነት የሚሆን ግንኙነት መፈጠር እንዳለበትም አውስተዋል።
አባል ሀገራቱ በተለይ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መስክ ተቀራርበው መሥራት እንደሚጠበቅባቸው ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ መልዕክት ያስተላለፉት።
ብሪክስ ፍትኃዊና አካታች የዓለም ሥርዓት ለመፍጠር ከፍተኛ ሚና እንደሚያበረክትም ተናግረዋል።
በተለይም ታዳጊ ሀገራት በዓለም አቀፍ መድረኮች ድምጻቸው እንዲሰማ በማድረግ ረገድ ሚናው የጎላ ስለመሆኑም ነው ያነሱት።
አፍሪካ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት ፍትኃዊ ውክልና እንዲኖራት በሚደረገው ጥረት ውስጥ የጉባኤው ተሳታፊ ሀገራት ተመሳሳይ አቋም እንደሚኖራቸውም ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።
የአፍሪካ ጥያቄ የውክልና ብቻ ሳይሆን የፍትኃዊነት ጉዳይ መሆኑንም ነው ጨምረው የገለጹት።
ከሳሃራ በታች 3ኛውን ግዙፍ ኢኮኖሚ የያዘችው ኢትዮጵያ ያላት ወጣት አምራች ኃይል፣ ለም መሬትና ታዳሽ ኃይል ምቹ የኢንቨስትመንት መዳራሻ እንደሚያደርጋትም ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ ተግባራዊ እያደረገችው የምትገኘው ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ አዳዲስ የዕድገት መንገዶችን መክፈቱንም እንዲሁ።
በሌላ በኩል ኢትዮጵያ እየተገበረችው ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የአየር ንብረት ልውጥን የማይበገር የኢኮኖሚ እድገት ለመገንባት ያላትን ቁርጠኝነት እንደሚያመላክትም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል።