በመንግስት በኩል ሚዲያው ለሚያከናውናቸው ስራዎች ሁለንተናዊ ድጋፎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ - ኢዜአ አማርኛ
በመንግስት በኩል ሚዲያው ለሚያከናውናቸው ስራዎች ሁለንተናዊ ድጋፎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ

አዲስ አበባ፤ ታኅሣሥ 25/2017(ኢዜአ)፦ በመንግስት በኩል ሚዲያው ለሚያከናውናቸው ስራዎች ሁለንተናዊ ድጋፎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለፁ።
ዛሬ በቅርቡ በይፋ ውህደት በፈጠሩት ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እና ዋልታ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን ኮርፖሬት በአሁኑ መጠሪያቸው ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ጉብኝት አካሂደናል ሲሉ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው አስፍረዋል።
ያሉንን አቅሞች እየደመርን ታላቅ ሀገርን ለመገንባት ሚዲያ ትልቅ አቅም አለው ብለዋል።
ተቋሙ በዘመናዊ መሳሪያዎችና በጥራት የተደገፉ ተግባራትን የሚያከናውን መሆኑን በአካል እንደተመለከቱ ገልጸዋል።
ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን የሁለት ጠንካራ ሚዲያ ድምር ውጤት በመሆኑ ወቅቱ የሚፈልገውን አቅምና ብቃት ተላብሶ ሀገርና ህዝብን የሚጠቅም ስራዎች መስራት እንደሚገባውም አመልክተዋል።
በዛሬ የሚዲያ ተቋሙ ምልከታችን በቀጣይ ድጋፍ የሚያሻቸው ጉዳዮች እንዳሉ ተመልክተናልም ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።
ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን በቀጣይ ዜናና ወቅታዊ፣ የምርመራና ማህበረሰብ ተኮር ስራዎችን ከተገቢ መረጃዎች ጋር ለህብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ስራዎችን አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባልም ብለዋል።
በመንግስት በኩል ሚዲያው ለሚያከናውናቸው ስራዎች ሁለንተናዊ ድጋፎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።