ደህንነቱ የተጠበቀ የዲጂታል ስነ ምህዳር ለመፍጠር ዓለም አቀፍ ትብብርን ማጠናከር ይገባል- አምባሳደር ልዑልሰገድ ታደሰ

አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 4/2017(ኢዜአ)፦ደህንነቱ የተጠበቀ የዲጂታል ስነ ምህዳር ለመፍጠር ዓለም አቀፍ ትብብር እና አጋርነትን ማጠናከር እንደሚገባ በብራዚል የኢትዮጵያ  አምባሳደር ልዑልሰገድ ታደሰ ገለጹ።

ኢትዮጵያ በብራዚል መዲና ብራዚሊያ በተካሄደው የብሪክስ የኢንፎርሜሽን እና ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ (አይሲቲ) ደህንነት እና ጥበቃ ስብሰባ ላይ ተሳትፋለች።

በብራዚል የኢትዮጵያ አምባሳደር ልዑልሰገድ ታደሰ ደህንነቱ የተጠበቀ የዲጂታል ምህዳር ለመፍጠር ሀገር አቀፍ ትብብር እና ዓለም አቀፍ አጋርነት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል።

አምባሳደሩ በስብሰባው ላይ ስለ ኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ፖሊሲ ገለጻ አድርገዋል።

ፖሊሲው የመንግስት፣ ህዝብ እና የበርካታ ባለድርሻ አካላት የጋራ ተሳትፎን ማዕከል ያደረገ፣ ለቁልፍ የመረጃ መሰረተ ልማቶች እና ለግል መረጃ ጥበቃ ትኩረት የሚሰጥ መሆኑን አመልክተዋል።

በተጨማሪም ለዲጂታል የኢኮኖሚ ተግባራት ደህንነቱ የጠበቀ አሰራርን መፍጠር የሚያስችል ነው ብለዋል።

ኢትዮጵያ በአይሲቲ ደህንነት ዓለም አቀፍ ትብብር እና አጋርነት እንዲጠናከር ቁርጠኛ ናት ብለዋል።

በብሪክስ ማዕቀፍ አማካኝነት የአይሲቲ ዘርፍ እድሎችን መጠቀም እና ስጋቶች በጋራ መከላከል እንደሚገባም ነው አምባሳደሩ ያሳሰቡት።

ስብሰባው የብሪክስ አባል ሀገራት የአይሲቲ ደህንነት ይዞ የመጣቸው እድሎች እና ፈተናዎች ላይ ሀሳቦችን እንዲለዋወጡ እና ሀገራዊ ተሞክሯቸውን እንዲያቀርቡ ምቹ አጋጣሚን መፍጠሩ ተመላክቷል።

አባል ሀገራቱ በጉዳዩ ላይ ብሪክስ ጠንካራ ትብብር መፍጠር እንዳለበት የጋራ መግባባት ላይ መድረሳቸውን በብራዚሊያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም