የቀድሞው ፕሬዝዳንት መንግሥቱ ሃይለማርያምን አውሮፕላን ጠግኖ ለአገልግሎት ማብቃት በሁሉም መስክ ውጤታማ ስራ የማከናወን ማሳያ ነው - ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ - ኢዜአ አማርኛ
የቀድሞው ፕሬዝዳንት መንግሥቱ ሃይለማርያምን አውሮፕላን ጠግኖ ለአገልግሎት ማብቃት በሁሉም መስክ ውጤታማ ስራ የማከናወን ማሳያ ነው - ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 8/2017(ኢዜአ)፦ የቀድሞው ፕሬዝዳንት አውሮፕላን ከ37 ዓመታት በኋላ ጠግኖ ለአገልግሎት ማብቃት በተቋሙ በሁሉም መስክ ውጤታማ ሥራ እየተሠራ ስለመሆኑ ማሳያ ነው ሲሉ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ገለጹ።
ከአገልግሎት ውጪ የነበረውን የቀድሞው ፕሬዝዳንት መንግሥቱ ሃይለ ማርያም አውሮፕላን ጠግኖ ጥቅም ላይ ማዋል መቻሉ ተገልጿል።
ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ እንደገለጹት የቀድሞውን የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት መንግሥቱ ሃይለማርያም አውሮፕላን ከተጣለበት ጥሻ በማንሳት አፕግሬድና ኦቨር ሆል በማድረግ ከ37 ዓመት በኋላ የበረራ አገልግሎት እንዲሠጥ ማድረግ ተችሏል።
ይሄም በመከላከያ ሰራዊት ተቋም ውስጥ በሁሉም መስክ ውጤታማ ሥራ እየተሠራ ስለመሆኑ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል።
አውሮፕላኑ አስፈላጊውን ጥገና አግኝቶ መብረር እና ወደ ኃይል መመለስ እንዲችል በሰጠነው መመሪያ መሠረት ለተሳተፋችሁ የአየር ሃይል አመራሮች ቴክኒሺያኖች የመከላከያ ድጋፍ ሰጪ ሁሉ አመሠግናለሁ ብለዋል።
የኢፌዴሪ አየር ሃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ በበኩላቸው አየር ሃይል በሰው ሃይል ግንባታ ፣ትጥቆችን ማሣደግና ከዘመኑ አቅም ላይ ማድረስ፣ መሠረተ ልማቶችን ተቋሙን በሚመጥን ልክ ማስፋፋት ትኩረት የተሠጠባቸው መሠረታዊ ነጥቦች መሆናቸውን ገልጸዋል።
አውሮፕላኑን ጠግኖ ወደ ኃይል መመለስም የዚሁ አንድ አካል ነው ብለዋል።
ዳሽ ፋይፍ ወይም ቡፋሎ በሚል መጠሪያ የሚታወቀውና ለቀድሞው የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት መንግስቱ ኃይለማርያም አገልግሎት ይሠጥ የነበረውን አውሮፕላን ከአንድ ዓመት ጊዜ በላይ አስፈላጊውን ጥገና በአየር ሃይል ቴክኒሺያኖች በመሥጠት ከሰላሣ ሰባት ዓመታት በኋላ ለበረራ ማብቃት እንደተቻለም ተናግረዋል።
ለትራንስፖርት ፣ለፓራሹት ዝላይ እና የካርጎ አገልግሎት መሥጠት የሚችለው አውሮፕላን ተጠግኖ ወደ ኃይል እንዲመለስ የተቋሙ ከፍተኛ አመራሮች ለሠጡት ድጋፍ ሙያተኞች ላደረጉት አበርክቶ ዋና አዛዡ ማመስገናቸውን ከመከላከያ ሰራዊት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።