ሶስተኛው የአፍሪካ ዌልዲንግ ፌዴሬሽን ጉባኤና ዓለም አቀፍ ኮንፈረንስ ተጠናቀቀ

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 8/2017(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው ሶስተኛው የአፍሪካ ዌልዲንግ ፌዴሬሽን ጉባኤ እና አለም አቀፍ ኮንፈረንስ ተጠናቋል።

ከሚያዝያ 6 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በዓድዋ ድል መታሰቢያ ሲካሄድ የቆየው ሶስተኛው የአፍሪካ ዌልዲንግ ፌደሬሽን ጉባኤና አለም አቀፍ ኮንፈረንስ የማጠቃለያ መርሃ-ግብር ተካሄዷል።

በማጠቃለያ መርሃ-ግብሩ ላይ የአፍሪካ ዌልዲንግ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ሐመድ አቡደል አሊም፣ የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብሩክ ከድር(ዶ/ር)ን ጨምሮ ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል።

በሶስተኛው የአፍሪካ ዌልዲንግ ፌዴሬሽን ጉባኤ እና አለም አቀፍ ኮንፈረንስ በአገራቱ መካከል የልምድ ልውውጥ የተደረገበት መሆኑ በዚሁ ወቅት ተገልጿል።

የአፍሪካ ዌልዲንግን በተመለከተ የተለያዩ ጥናታዊ ጽሁፎች ቀርበው ውይይት መደረጉም ታውቋል።

አፍሪካ በዌልዲንግ ዘርፍ ያላት ከፍተኛ አቅም የተዳሰሰ ሲሆን ሀገራት ዘርፉን ለማሳደግ በጋራ እንዲሰሩ ጥሪ የተደረገበት መሆኑ ተጠቁሟል።

ተሳታፊዎቹ በቆይታቸው ዓድዋ ድል መታሰቢያ እና አዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬሽን ማዕከልን ጨምሮ የተለያዩ በከተማው የተሰሩ የልማት ስራዎችን መጎብኘታቸው ተገልጿል።

በዌልዲንግ ክህሎት ተወዳድረው አሸናፊ ለሆኑ ተወዳዳሪዎች ሽልማት ተበርክቷል።

አራተኛው የአፍሪካ ዌልዲንግ ፌደሬሽን ጉባኤ በደቡብ አፍሪካ እንደሚካሄድ ታውቋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም