የሀገራችንን የአየር ክልል ከማንኛውም ጥቃት ከመጠበቅ ባለፈ ታሪክን የማደስ ተግባራችንን አጠናክረን እንቀጥላለን - ሌተናል ጀነራል ይልማ መርዳሳ - ኢዜአ አማርኛ
የሀገራችንን የአየር ክልል ከማንኛውም ጥቃት ከመጠበቅ ባለፈ ታሪክን የማደስ ተግባራችንን አጠናክረን እንቀጥላለን - ሌተናል ጀነራል ይልማ መርዳሳ

አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 10/2017(ኢዜአ)፦ የሀገራችንን የአየር ክልል ከማንኛውም ጥቃት ከመጠበቅ ባለፈ ታሪክን የማደስ ተግባራችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ የኢፌዴሪ አየር ሀይል አዛዥ ሌተናል ጀነራል ይልማ መርዳሳ ገለጹ።
ሌተናል ጀነራል ይልማ መርዳሳ ከሰላሳ ሰባት ዓመት በላይ ከአገልግሎት ውጪ ሆኖ የቆየውንና የቀድሞ የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት መንግስቱ ኃይለማሪያም ይንቀሳቀሱበት የነበረው የDHC-5 Buffalo አውሮፕላንን ጥገናና ማሻሻል በማድረግ ወደ ስራ ላስገቡ ኢንጂነሮችና ቴክኒሺያኖች ምስጋና አቅርበዋል።
አውሮፕላኑ ሙሉ ጥገና የተካሄደለትና ከዘመኑ ጋር የተዋሀዱ ቴክኖሎጂዎች የተገጠሙለት መሆኑን ማረጋገጣቸውንና በተደጋጋሚ ሙከራ ወደ ሀይል እንዲቀላቀል በመደረጉ መደሰታቸውን መግለጻቸውን ከመከላከያ ሰራዊት የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
አዛዡ፤ በተቋሙ የሚመራመሩና ተአምር የሚፈጥሩ ወጣቶች መኖራቸውን ያየንበትም ነው ሲሉ መናገራቸውም በመረጃው ተጠቁሟል።
መከላከያ ትጥቆችን ከመግዛት በተጨማሪ አምራች ለመሆን እያደረገ ባለው ጥረት ከፍተኛ ውጤቶች እየተገኙ መሆኑን የገለፁት አዛዡ፤ አንጋፋው የአየር ሀይልም የዚሁ አካል በመሆን በተለያዩ ዘርፎች የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመንደፍ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝም አረጋግጠዋል።
ለታላቅ ሀገር፣ ታላቅ የአየር ሀይል በሚል መርህ የተገነባው የአየር ሀይል የሀገራችንን የአየር ክልል ከመጠበቅ ባለፈ ታሪኩን እያደሰና ዘመኑን የዋጀ ተግባራትን እያከናወነ ሀገራዊ አቅም የመሆን ተግባሩን አጠናክሮ መቀጠሉንም ገልጸዋል።
በአየር ሀይል ቴክኒሺያኖች ጥገናና መሻሻል ተደርጎለት ወደ ሀይል የተቀላቀለውና የካናዳ ስሪት የሆነው የDHC-5 Buffalo አውሮፕላን የቀድሞ የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ከሀገር ሲሸሹ እስከ ኬንያ የሄዱበት አውሮፕላን መሆኑ ታሪካዊ ያደርገዋል ሲልም መከላከያ በማህበራዊ ትስስር ገጹ ባወጣው መረጃ አመላክቷል።