ኢትዮጵያ እና ቬይትናም አረንጓዴ ኢኮኖሚ የመገንባት ራዕይ ይዘው እየሰሩ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ እና ቬይትናም አረንጓዴ ኢኮኖሚ የመገንባት ራዕይ ይዘው እየሰሩ ነው

አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና ቬይትናም አረንጓዴ ኢኮኖሚ የመገንባት ራዕይ ይዘው እየሰሩ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ(ዶ/ር) ገለጹ።
የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የቬይትናም ቆይታን አስመልክቶ የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ(ዶ/ር) ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በማብራሪያቸውም ቬይትናም ከ20 እና 30 ዓመት በፊት በጦርነት የተጎዳች ሀገር ብትሆንም አሁን ላይ መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ መሰለፏን አንስተዋል።
ኢትዮጵያ የልማት ትልሟን ለማሳካት የረጅም፣ የመካከለኛ እና የአጭር ጊዜ ዕቅድ አውጥታ እየሰራች መሆኑን ጠቅሰው፣ ቬይትናምም በተመሳሳይ የልማት ዕቅዷን ለማሳካት ባደረገችው ትጋት ውጤታማ ሆናለች ብለዋል።
ሀገሪቱ በኢንዱስትሪና ኮንስትራክሽን ዘርፎች ባሳየችው እመርታ የዓለም የምርት ማዕከል መሆን መቻሏንም ነው ያነሱት፡፡
ለዚህ ውጤት መመዝገብ ዕቅድን በአግባቡ ለመፈጸም መንግስት ያሳየው ቁርጠኝነትና የህዝብ ድጋፍ መሆኑን ነው ያነሱት።
ኢትዮጵያም በአጭር ጊዜ ውስጥ ብልጽግናዋን ለማረጋገጥ እያደረገች ያለችው ጥረት ውጤታማ እንደሚሆን ከቬይትናም ልምድ የወሰደችበት ነው ብለዋል።
እንደ ሚኒስትር ዴኤታው ገለጻ፤ ኢትዮጵያ እና ቬይትናም አረንጓዴ ኢኮኖሚ የመገንባት ተመሳሳይ ራዕይ ይዘው እየሰሩ መሆኑን ነው የተናገሩት።
ኢትዮጵያ ንጹህ፣ አረንጓዴ፣ ለኑሮ አመቺና ዘላቂ ከተማ ለመገንባት እያደረገች ያለችው ጥረት ከቬይትናም ጋር እንደሚያመሳስላትም ገልጸዋል።
በጉብኝቱ ስማርት ሲቲ ግንባታ ላይ ቬይትናም ያላትን ልምድ መቅሰም መቻሉንም ነው ዶክተር እዮብ ተካልኝ ያብራሩት።