ከአነስተኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች መስፈንጠር እንደሚቻል ከቬይትናም ተሞክሮ መቅሰም ተችሏል - ኢዜአ አማርኛ
ከአነስተኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች መስፈንጠር እንደሚቻል ከቬይትናም ተሞክሮ መቅሰም ተችሏል
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2017(ኢዜአ)፦ ከአነስተኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች መስፈንጠር እንደሚቻል ከቬይትናም ተሞክሮ መቅሰም መቻሉን የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍስሃ ይታገሱ(ዶ/ር) ገለጹ።
የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍስሃ ይታገሱ(ዶ/ር) የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የቬይትናም ቆይታን አስመልክቶ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በማብራሪያቸውም ቬይትናም በጥቂት ዓመታት ውስጥ በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ከፍተኛ እመርታን ካስመዘገቡ ሀገራት መካከል አንዷ ናት ብለዋል፡፡
በተለይም የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትን በመሳብ አማራጭ የኢንቨስትመንት ማዕከል በመሆን ትልቅ ዕድገት ማስመዝገቧን ጠቁመው፤ በዚህም የአምራች ዘርፉ በኢኮኖሚው ውስጥ ያለው ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል።
ከቬይትናም በአጭር ጊዜ ውስጥ ኢንዱስትራላይዜሽንን ለማስፋት የሄዱበት መንገድ በተሞክሮነት የሚወሰድ መሆኑን ተናግረዋል።
በተለይም በዓለም አቀፍ የማኑፋክቸሪንግ እሴት ሰንሰለት ውስጥ የሚኖር ጂኦፖለቲካዊ አካሄዶችን በማየት የወሰዱት እርምጃ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳቡንና ይህም ትልቅ ትምህርት የተወሰደበት መሆኑን አንስተዋል።
ትልቅ ትምህርት የተወሰደበት ዓለም አቀፍ ሁኔታዎችንና አዝማሚያዎችን በመተንተን ኢንዱስትሪዎች ወደ ሀገር እንዲመጡ መሳብ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም ቬይትናምን የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የስበት ማዕከል እንድትሆን አስችሏታል ብለዋል።
እንዲሁም ከትንንሽ ኢንዱስትሪዎች ወደ ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች መስፈንጠር እንደሚቻልም ከቬትናም ተሞክሮ መቅሰም መቻሉን ገልጸዋል።
ኢንዱስትሪዎች በሀገር ውስጥ ግብዓት እንዲጠቀሙ ክትትል እና ድጋፍ ማድረግ እንደሚገባም ነው ዶክተር ፍሰሃ ያብራሩት።