በቬይትናም በሩዝ ምርት እና የእሴት ሰንሰለት ላይ በጋራ ሰፋፊ ስራዎችን መስራት የሚያስችሉ ስምምነቶች ተደርገዋል - ሚኒስትር ግርማ አመንቴ(ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
በቬይትናም በሩዝ ምርት እና የእሴት ሰንሰለት ላይ በጋራ ሰፋፊ ስራዎችን መስራት የሚያስችሉ ስምምነቶች ተደርገዋል - ሚኒስትር ግርማ አመንቴ(ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2017(ኢዜአ)፦ በቬይትናም ቆይታ በሩዝ ምርት እና የእሴት ሰንሰለት ላይ በጋራ ሰፋፊ ስራዎችን መስራት የሚያስችሉ ስምምነቶች መደረጋቸውን የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ(ዶ/ር) ገለጹ።
ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ(ዶ/ር) የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የቬይትናም ቆይታን አስመልክቶ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በማብራሪያቸውም ቬይትናም በአጭር ጊዜ ውስጥ ቀጣይነት ያለው እድገት በማስመዝገብ መካከለኛ ገቢ ወዳላቸው ሀገራት የገባች መሆኗን አንስተዋል።
በተለይም የግብርና ልማቷን በማዘመን ትልቅ እድገት ማስመዝገቧን ተናግረዋል።
ባለፉት 20 እና 30 አመታት በግብርና ላይ በሰራችው ስራ አሁን ላይ በአለማችን ከፍተኛ የቡና አምራች እና ላኪ ሀገር መሆን መቻሏንም ገልጸዋል።
ኢትዮጵያም አንዷ ከፍተኛ የቡና አምራች ሀገር መሆኗን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ ቬይትናም በሩዝ እና በአትክልት እንዲሁም ፍራፍሬ ትልቅ አቅም መፍጠሯን አንስተዋል።
ቡና ኤክስፖርት በማድረግ 4 ቢሊዮን ዶላር እንደምታገኝ ጠቅሰው፤ ከዚህም ብዙ ልምድ መውሰድ እንደሚቻል ተናግረዋል።
የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ አንጻርም በተለይ በሩዝ ላይ ትልቅ ስራ መስራቷን ለመመልከት መቻሉን ገልጸዋል።
በ7 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ሩዝ በማልማት 24 ሚሊዮን ቶን ምርት እንደምታገኝ ተናግረዋል።
ኢትዮጵያም ባለፉት ሁለት አመታት ወደ 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ሩዝ ማምረት መጀመሯን በመግለጽ።
በቬይትናም ቆይታም በስንዴ የተሰራውን ስራ በሩዝ ላይ መድገም የሚያስችል የተሞክሮ ልውውጥ ማድረግ የሚያስችል ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን አንስተዋል።
በሩዝ ምርት እና የእሴት ሰንሰለት ላይ በጋራ ሰፋፊ ስራዎችን መስራት የሚያስችሉ ስምምነቶች መደረጋቸውንም ጨምረው ገልጸዋል።
ከአትክልት እና ፍራፍሬ ስራዎች አንጻር የሚወሰደው ተሞክሮ ምርቶቹ ሳይበላሹ የሚጓጓዙበት ስርዓት መሆኑን ጠቅሰዋል።
በተጨማሪም ምርቶቹን ከመነሻቸው ጀምሮ የሚሰበሰቡበት መንገድም ልምድ የሚወሰድበት መሆኑን እና ይህም የድህረ ምርት ብክነት የቀነሱበትን መንገድ እንደሚያሳይም ተናግረዋል።
በታዳሽ ሀይል፣ በስማርት ሲቲ ግንባታ እንዲሁም ከተፈጥሮ ጋር የተላመደ የአኗኗር ዘዴያቸው አስደናቂ መሆኑን በመጥቀስ።
ቀጣይነት ያላቸውን ስራዎች ማከናወን ከተቻለ በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ አደገ ኢኮኖሚ መሻገር እንደሚቻል ቬይትናም ማሳያ መሆኗንም ተናግረዋል።