ኮሌጁ የግብርና ስራዎችን የሚያቀላጥፉ የተለያዩ የፈጠራ ውጤቶችን ይፋ አደረገ - ኢዜአ አማርኛ
ኮሌጁ የግብርና ስራዎችን የሚያቀላጥፉ የተለያዩ የፈጠራ ውጤቶችን ይፋ አደረገ

ጅማ፤ሚያዚያ 12/2017 (ኢዜአ)፦የጅማ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የግብርና ስራዎችን የሚያቀላጥፉ የተለያዩ የፈጠራ ውጤቶችን ይፋ አደረገ።
የጅማ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዲን መሀመድ አብደላ፤ ኮሌጁ በተለይም የግብርናውን ዘርፍ የሚያግዙ ፈጠራዎች ላይ በማተኮር እየሰራ ይገኛል ብለዋል።
በዚህም የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽ ባልሆነባቸው አካባቢዎች አርሶ አደሮች በማንዋል የሚሰሩባቸው ቀላል ማሽነሪዎች መፍጠር መቻሉን አንስተዋል።
የበቆሎ መፈልፈያ፣ እና የሩዝ መውቂያ፣ የመኖ መፍጫና ሌሎችም ቀላል ማሽነሪዎች ከኮሌጁ ፈጠራዎች መካከል መሆናቸውን ዲኑ ጠቅሰዋል።
እነዚህ ማሽኖች በፍጥነት ስራዎች እንዲጠናቀቁ በማድረግ የአርሶ አደሮችን ጊዜና ጉልበት ከመቆጠብም ባለፈ የምርት ብክነትን የሚያስቀሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በብዛት ከተመረቱ በኋላ ለተጠቃሚዎች በተመጣጣኝ ዋጋ የማቅረብ እቅድ መኖሩን ጠቁመው፥ የግብርናውን ዘርፍ የሚያግዙ ፈጠራዎች ላይ በማተኮር የፈጠራ ስራው ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ገልጸዋል።
ከኮሌጁ መምህራን መካከል ዋሲሁን ደሳለኝ የፈጠራ ውጤቶቹ በተለይም ለአርሶ አደሩ አጋዥ መሆናቸውን ጠቅሰው፥ ለአገልገሎት እንዲበቁ ማድረግ አስፈላጊ ነው ብለዋል።
በቀጣይም የግብርናውን ዘርፍ የሚያግዙ ቀላል ማሽነሪዎችን በመፍጠር የግብርና ስራዎችን ለማቅለል የሚያስችሉ ፈጠራዎች ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑን አረጋግጠዋል።