የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከተጀመረ በኋላ የሚመረቱ ምርቶች ጥራታቸውና ተወዳዳሪነታቸው እያደገ መጥቷል - ሚኒስትር መላኩ አለበል - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከተጀመረ በኋላ የሚመረቱ ምርቶች ጥራታቸውና ተወዳዳሪነታቸው እያደገ መጥቷል - ሚኒስትር መላኩ አለበል

አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 13/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ይፋ ከተደረገ ጀምሮ የሚመረቱ ምርቶች ከአመት አመት አይነታቸው ጥራታቸው እና ተወዳዳሪነታቸው እያደገ መምጣቱን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን ሚያዚያ 29 ቀን 2014 ዓ.ም ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል።
ንቅናቄው በኢትየጵያ የተለያዩ ምርቶች እንዲመረቱ ከማስቻሉም በተጨማሪ ኢትዮጵያ ከውጭ የምታስገባቸውን ምርቶች በማስቀረት በኩል ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል፡፡
ሚኒስትር መላኩ አለበል ለኢዜአ እንደገለጹት የኢትየጵያ ታምርት ንቅናቄ ይፋ ከተደረገ ጀምሮ ባለፉት አመታት በርካታ ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል፡፡
በዚህም ምርቶች ገበያ እንዲያገኙ እንዲሁም ትስስር አንዲፈጠርላቸው በማድረግ በኩል ትልቅ ሚና መጫወቱን ገልጸዋል፡፡
ባለፉት ሶስት ዓመታት የሚመረቱ ምርቶች ከአመት አመት አይነታቸው ጥራታቸውና ተወዳዳሪነታቸው እያደገ መምጣቱንም አስታውቀዋል፡፡
መንግስት ለማኑፋክቸሪንግ ትልቅ ትኩረት በመስጠት በዘርፉ የሚስተዋለውን የቅንጅት ችግር መቀረፉንም አስረድተዋል፡፡
ይህንን ተከትሎም አምራቾች ውጤታማ የማምረት ስራ ውስጥ መግባት መቻላቸውን አስታውቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን የበለጠ ውጤታማ ለማድረግ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመው፤ የማኑፋክቸሪንግ ካውንስል መቋቋሙና ወደ ስራ መግባቱን ለአብነት ጠቅሰዋል።