በምስራቅ ጎጃም ዞን የወተትና የሥጋ ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው - ጽህፈት ቤቱ

ደብረ ማርቆስ፤ ሚያዚያ 13/2017(ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን የእንስሳት ዝርያን በማሻሻል የወተትና የሥጋ ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ እንስሳትና አሳ ሃብት ተጠሪ ጽህፈት ቤት አስታወቀ።

በጽህፈት ቤቱ የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ቡድን መሪ አቶ ጤናው ወንድም አማሽ ለኢዜአ እንደገለጹት በዞኑ አርሶ አደሩን ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በእንስሳት ሃብት ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ።

በበጀት ዓመቱ የግብርና ቴክኖሎጂን በመጠቀም ከ54ሺህ በሚበልጡ ላሞች ላይ የዝርያ ማሻሻል ሥራ ለመስራት ታቅዶ በ9ኝ ወሩ ከ19ሺህ በላይ ላሞች ላይ የማዳቀል ሥራ መከናወኑን ገልጸዋል።

በኮርማ በማስጠቃትና በዘመናዊ የማዳቀያ መንገዶች ከተዳቀሉ ላሞችም ዝርያቸው የተሻሻሉ ከ9ሺህ 400 በላይ ጥጆች መወለዳቸውን አብራርተዋል።

ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከአምስት ሺህ በላይ ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል።

ዝርያቸው የተሻሻሉ ለሞችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ በማድረግ የሌማት መርሀ ግብርን እውን ለማድረግ እየተሰራ መሆን ያስታወቁት ቡድን መሪው፣ የዝርያ ማሻሻል ሥራው የአካባቢው ላሞች በቀን ይሰጡት የነበረን ከሁለት ሊትር በታች የወተት ምርት በቀን ከ10 ሊትር በላይ ወተት ለማምረት ማስቻሉን ገልጸዋል።

በሥጋ ምርትም ዝርያቸው ከተሻሻሉ ከብቶች በአማካይ እስከ 30 ኪሎ ግራም ጭማሬ እንዳለው ጠቁመው፣ ይህም የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት እንደሚያሳድገው አስገንዝበዋል።

በአነደድ ወረዳ የአምበር ከተማ ነዋሪ አቶ ሙሉሰው ማስረሻ በበኩላቸው እንደገለጹት፣ ከዚህ በፊት ከተዳቀሉ ሁለት ላሞች በቀን እስከ 18 ሊትር የወተት ምርት በማግኘት ከሽያጩ ገቢያቸውን እያሳደገ መምጣታቸውን ተናግረዋል።

ከወተት ልማት ያላቸውን ተጠቃሚነት ለማሳደግም ሁለት ላሞቻቸውን በተሻሻሉ ኮርማዎች ማዳቀላቸውን ጠቁመዋል።

በእዚሁ ወረዳ የጉዳለማ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ደርብ ካሳ በበኩላቸው ዝርያቸው የተሻሻሉ ላሞችን በማርባት  ከወተት ሽያጭ በተጨማሪ ጥጆችን በመሸጥ ተጠቃሚ መሆናቸውን አስረድተዋል።

ከዞኑ እንስሳትና አሣ ሃብት ተጠሪ ጽህፈት ቤት የተገኘው መረጃ እንደሚያሳያው በዞኑ ቁጥራቸው እስከ 200 ሺህ የሚደርሱ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው እንስሳት ይገኛሉ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም