ለውጭ ባለሃብቶች ዝግ የነበሩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች መከፈት በርካታ ኢንቨስተሮች ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ አስችሏል – የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 13/2017 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ዝግ የነበሩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች መከፈታቸው በርካታ የውጭ ባለሃብቶች ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ ማስቻሉን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ገለጸ፡፡

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ኢትዮጵያ ባለፉት ሰባት ዓመታት በበርካታ የለውጥ ሂደት እያለፈች አመርቂ ውጤቶችን ማስመዝገብ መቻሏን ጠቅሰዋል፡፡

ኮሚሽነሩ እንዳሉት፥ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ለውጭ ባለሃብቶች ዝግ የነበሩ ዘርፎች መከፈታቸውን ጠቁመው፥ በኢኮኖሚ ሪፎርሙ ኢንቨስትመንትን ሊደግፉ የሚችሉ ማሻሻያዎች መደረጋቸውን ተናግረዋል፡፡

የኢንቨስትመንት ህግን በማሻሻል ረገድ የተወሰዱ እርምጃዎች ከዚህ ቀደም ለውጭ ባለሃብቶች ተገድበው የቆዩ ዘርፎችን የከፈተ መሆኑን አንስተዋል።

የኢትዮጵያ የኢንቨስትመንት ቦርድ የውጭ ኩባንያዎች በጅምላ፣ ችርቻሮ እንዲሁም በወጪ እና ገቢ ንግዶች ላይ እንዲሰማሩ መፍቀዱን ጠቅሰዋል።

መንግስት ለረጅም አመታት ለውጭ ኩባንያዎች ዝግ ሆነው የቆዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎችን ክፍት ማድረጉ ለአብነትም እንደ ኢትዮ ቴሌኮምና የልዩ ኢኮኖሚ ዞን አዋጅ ኢንቨስትመንቱን የሚደግፉና የውጭ ባለሀብቶች በብዛት መጥተው እንዲሳተፉ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡

የኢንቨስትመንት ኮሚሽኑ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከፍተኛ አፈጻጸም ማስመዝገቡን የገለጹት ኮሚሽነሩ፥ ለአብነትም በውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ከአምናው የ2 ነጥብ 4 በመቶ ዕድገት ያለው መሳብ መቻሉን ገልጸዋል፡፡

ከሪፎርሙ አንጻር ኢትዮጵያ ካላት እምቅ አቅም አንጻር ከዚህም በላይ መጓዝ እንደሚገባ ጠቁመው፥ የጅምላና ችርቻሮ ወጪና ገቢ ንግድ መከፈቱን ተከትሎ ለ40 የውጭ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰጠቱን ተናግረዋል፡፡

36 የሚሆኑት ደግሞ በሂደት ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ቦርድ አጠቃላይ በኢትዮጵያ ያሉ ኢንዱስትሪ ፓርኮችን ወደ ልዩ ኢኮኖሚ ዞንነት የማሸጋገር ስልጣን ያለው መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የድሬዳዋ ነጻ ንግድ ቀጣና በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተመርቆ ስራ ከጀመረ ወዲህ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ባለሃብቶችን ወደ ቀጣናው እንዲገቡ እያደረገ እንደሚገኝም ገልጸዋል፡፡

በዚህም 11 የሚሆኑ ባለሃብቶች የገቡ ሲሆን አንዳንዶች ሸቀጦችን ጭምር እያመጡ መሆኑን ጠቁመዋል።

መንግስት ዝግ የነበሩ የፋይናንስ፣ የቴሌኮምና የንግድ ዘርፎችን ሪፎርም በማድረጉ ከፍተኛ ለውጥ እንዲመዘገብ እያስቻለ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም