አየር መንገዱ እ.አ.አ በ2025 ራዕዩ በአውሮፕላን ቁጥር እና መዳረሻ ብዛት የያዘውን እቅድ አስቀድሞ አሳክቷል - አቶ መስፍን ጣሰው

አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 13/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ እ.አ.አ 2025 ራዕዩ በአውሮፕላን ቁጥር እና በመዳረሻ ብዛት የያዘውን እቅድ አስቀድሞ ማሳካቱን የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው ገለጹ።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው በቢቢሲ ፎከስ ኦን አፍሪካ ፕሮግራም ከጅዌል ኪሪዩንጊ ጋር ቆይታ አድርገዋል።

በቆይታቸውም አየር መንገዱ እ.አ.አ በ2025 ራዕዩ በአውሮፕላን ቁጥር እና በመዳረሻ ብዛት የያዘውን እቅድ አስቀድሞ ማሳካቱን ተናግረዋል።

አየር መንገዱ እ.አ.አ በ2023/24 ሰባት ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ ገቢ ማግኘቱንና እስከ እ.አ.አ ጁን 2025 ባለው ጊዜ ገቢው 8 ቢሊዮን ዶላር ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል።

አየር መንገዱ ከቦይንግ ኩባንያ ጋር ያለው ትብብር አውሮፕላን ከመግዛት የገዘፈ መሆኑን ጠቁመው ቦይንግ ለሚያመርታቸው አዳዲስ አውሮፕላኖች የሚሆን የመለዋወጫ እቃዎችን እያቀረበ መሆኑን አንስተዋል።

አየር መንገዱ አቅሙን እና ተደራሽነቱን ለማስፋት እያከናወነ ያለውን ስራ አስመልክቶም አቶ መስፍን ማብራሪያ ሰጥተዋል።

በዚህም ኩባንያው በአፍሪካ ግዙፍ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ለመገንባት ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል።

የቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ የመጨረሻ የማስተናገድ አቅሙ ላይ ደርሷል ያሉት ዋና ስራ አስፈጻሚው ዓመታዊ የተሳፋሪ የማስተናገድ አቅሙ 25 ሚሊዮን መድረሱን አንስተዋል።

አዲስ አየር ማረፊያ መገንባት ያስፈለገውም በአቪዬሽን ዘርፉ በፍጥነት እያደገ ላለው ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት መሆኑንም ነው የተናገሩት።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም