ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ይጫወታል
Apr 22, 2025 13
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 14/2017 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ጨዋታውን ያካሂዳል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከቀኑ 9 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ መድን በ48 ነጥብ የአንደኝነት ደረጃውን ተቆናጧል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ29 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። መድን ካሸነፈ ከተከታዩ ባህር ዳር ከተማ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ 11 ከፍ ያደርጋል። ለኢትዮ ኤሌክትሪክ ማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና ስፍራ ለመራቅ ያስችለዋል። የ26ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር ሃዋሳ ከተማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ምሽት 12 ሰዓት ላይ ያገናኛል። ሃዋሳ ከተማ በ24 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የአምናው የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ35 ነጥብ 7ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በተያያዘም ትናንት በተካሄዱ የ26ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ጨዋታዎች ባህር ዳር ከተማ መቀሌ 70 እንደርታ 4 ለ 1 ፣ መቻል አዳማ ከተማን 2 ለ 0 እንዲሁም ድሬዳዋ ከተማ ፋሲል ከነማን 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
ኖቲንግሃም ፎረስት ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Apr 21, 2025 56
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2017(ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር ኖቲንግሃም ፎረስት ቶተንሃም ሆትስፐርስን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በለንደን ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኤሊዮት አንደርሰን እና ክሪስ ውድ የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሪቻርልሰን ለቶተንሃም ብቸኛዋን ጎል አስቆጥሯል። ድሉን ተከትሎ ኖቲንግሃም ፎረስት በ60 ነጥብ ደረጃውን ከ5ኛ ወደ 3ኛ ከፍ አድርጓል። በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የተሳትፎ ህልሙን ለማሳካት በሚያደርገው ጉዞ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ37 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ለአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ የሚደረገው ጠንካራ ፉክክር ይበልጥ አጓጊ ሆኗል። በተያያዘም ዛሬ በእንግሊዝ ሻምፒዮን ሺፕ የተደረጉ ጨዋታዎችን ተከትሎ ሊድስ ዩዩናይትድ እና በርንሌይ ወደ እንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ማደጋቸውን አረጋግጠዋል።
ባህር ዳር ከተማ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ ያደረገበት ወሳኝ ድል አስመዝግቧል
Apr 21, 2025 69
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2017(ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ መቀሌ 70 እንደርታን 4 ለ 1 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቸርነት ጉግሳ እና አቤል ማሙሽ በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አሸናፊ ሐፍቱ ለመቀሌ 70 እንደርታ ብቸኛዋን ጎል አስቆጥሯል። ድሉን ተከትሎ ባህር ዳር ከተማ በ40 ነጥብ ደረጃውን ከ3ኛ ወደ 2ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱም 11ኛ ድሉን ማስመዝገብ ችሏል። ከሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነትም ወደ ስምንት ዝቅ ማድረግ ችሏል። በሊጉ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው መቀሌ 70 እንደርታ በ28 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረጉ የ26ኛ ሳምንት ሌሎች ጨዋታዎች መቻል አዳማ ከተማን 2 ለ 0 እንዲሁም ድሬዳዋ ከተማ ፋሲል ከነማን 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
ድሬዳዋ ከተማ ድል ቀንቶታል
Apr 21, 2025 61
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2017(ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ድሬዳዋ ከተማ ፋሲል ከነማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አስራት ቶንጆ በ54ኛው ደቂቃ የማሸነፊያዋን ጎል አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ ድሬዳዋ ከተማ በ29 ነጥብ ደረጃውን ከ14ኛ ወደ 12ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱም ስድስተኛ ድሉን አሳክቷል። በአንጻሩ በሊጉ 7ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ፋሲል ከነማ በ33 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ባህር ዳር ከተማ ከመቀሌ 70 እንደርታ ይጫወታሉ።
መቻል ደረጃውን ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል
Apr 21, 2025 64
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 13/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሃ ግብር መቻል አዳማ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። ረፋድ ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሽመልስ በቀለ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ መቻል በ38 ነጥብ ደረጃውን ከ6ኛ ወደ 3ኛ ከፍ ያደረገ ሲሆን በሊጉ 10ኛ ድሉን አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ 13ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የ26ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ከሰዓት በኋላ ቀጥሎ ሲውል ፋሲል ከነማ ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት፣ ባህር ዳር ከተማ ከመቀሌ 70 እንደርታ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
በፕሪሚየር ሊጉ ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ
Apr 21, 2025 67
አዲስ አበባ ፤ሚያዚያ 13/2017 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። የመጀመሪያው ጨዋታ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ከ30 በአዳማ ከተማ እና መቻል መካከል በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይከናወናል። አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። መቻል በ35 ነጥብ 6ኛ ደረጃን ይዟል። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ፋሲል ከነማ ከድሬዳዋ ከተማ ይጫወታሉ። ፋሲል ከነማ በ33 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ሲይዝ ድሬዳዋ ከተማ በ26 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የዕለቱ የመጨረሻ ጨዋታ ምሽት 12 ሰዓት ላይ ባህር ዳር ከተማ እና መቀሌ 70 እንደርታን ያገናኛል። ባህር ዳር ከተማ በ37 ነጥብ 3ኛ ደረጃን ይዟል። መቀሌ 70 እንደርታ በ28 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በተያያዘ ዜና ትናንት በተደረጉ የ26ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 ሲያሸንፍ አርባምንጭ ከተማ እና ስሑል ሽሬ ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይተዋል።
ሊቨርፑል የሊጉን መሪነት ያጠናከረበት ወሳኝ ድል አስመዝግቧል
Apr 20, 2025 95
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 12 /2017 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሊቨርፑል ሌይስተር ሲቲን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኪንግ ፓወር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ትሬንት አሌክሳንደር አርኖልድ በ76ኛው ደቂቃ የማሸነፊያዋን ጎል ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ውጤቱን ተከትሎ ሊቨርፑል ነጥቡን ወደ 79 ከፍ በማድረግ የሊጉን መሪነት አጠናክሯል። ከተከታዩ አርሰናል ጋር ያለው የነጥብ ልዩነት በድጋሚ ወደ 13 ከፍ አድርጓል። ቀያዮቹ ዋንጫውን ለማንሳት የተቃረቡበትንም ወሳኝ ድል አስመዝግበዋል። ሌይስተር ሲቲ በ18 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሽንፈቱን ተከትሎ ሌይስተር ሲቲ አምስት ጨዋታ እየቀረ ከሳውዝሃምፕተን ቀጥሎ ከሊጉ የወረደ ሁለተኛ ክለብ ሆኗል።
አርባምንጭ ከተማ እና ስሑል ሽሬ ነጥብ ተጋርተዋል
Apr 20, 2025 79
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 12 /2017 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 26ኛ ሳምንት አርባምንጭ ከተማ እና ስሑል ሽሬ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ምንም ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ጨዋታው ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተካሂዷል። ውጤቱን ተከትሎ አርባምንጭ ከተማ በ35 ነጥብ 8ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ስሑል ሽሬ በ18 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቀን ላይ በተደረገ ጨዋታ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል።
አርሰናል ኢፕስዊች ታውንን አሸነፈ
Apr 20, 2025 88
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 12/2017 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት ጨዋታ አርሰናል ኢፕስዊች ታውንን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። በፖርትማን ሮድ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሊያንድሮ ትሮሳርድ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ጋብርኤል ማርቲኔሊ እና ኢታን ንዋኔሪ ቀሪዎቹን ጎል ለመድፈኞቹ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የኢፕስዊች ታውኑ ተከላካይ ሌፍ ዴቪስ በ32ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ውጤቱን ተከትሎ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አርሰናል ነጥቡን ወደ 66 ከፍ አድርጓል። ከሊጉ መሪ ጋር ያለውን ልዩነት በጊዜያዊነት ወደ 10 ዝቅ አድርጓል። ኢፕስዊች ታውን በ21 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በሌሎች ጨዋታዎች ማንችስተር ዩናይትድ በሜዳው በዎልቭስ የ1 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። ቼልሲ ከሜዳው ውጪ ከመመራት ተነስቶ ፉልሃምን 2 ለ 1 አሸንፏል። ምሽት 12 ሰዓት ከ30 ላይ ሌይስተር ሲቲ የሊጉን መሪ ሊቨርፑል ያስተናግዳል።
ሲዳማ ቡና ድል ቀንቶታል
Apr 20, 2025 67
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 12/2017 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን 1ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፍቅረየሱስ ተክለብርሃን በ13ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ጎሏን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ሲዳማ ቡና በ35 ነጥብ ደረጃውን ከ11ኛ ወደ 8ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 9ኛ ድሉን አሳክቷል። በአንጻሩ በሊጉ 7ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ቡና በ39 ነጥብ 2ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ አርባምንጭ ከተማ ከስሑል ሽሬ ይጫወታሉ።
ወላይታ ድቻ በአፍሪካ የቮሊቦል ክለቦች ሻምፒዮና የመጀመሪያ ጨዋታውን ያደርጋል
Apr 20, 2025 56
አዲስ አበባ ፤ሚያዚያ 12/2017 (ኢዜአ)፡- ወላይታ ድቻ በ46ኛው የአፍሪካ የወንዶች የቮሊቦል ክለቦች ሻምፒዮና የመጀመሪያ ጨዋታውን ዛሬ ከሊቢያው ኢትሃድ ትሪፖሊ ጋር ያደርጋል። በሊቢያ ሚስራታ ከተማ የሚካሄደው ሻምፒዮና ትናንት ተጀምሯል። በሻምፒዮናው ላይ 25 የአፍሪካ የቮሊቦል ክለቦች ተሳታፊ ሆነዋል። ክለቦቹ በአራት ምድብ ተከፍለው ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያን ወክሎ በሻምፒዮናው የሚሳተፈው ወላይታ ድቻ በምድብ ሶስት ከሞሪሺየሱ ኦሊምፒክ ዲ ኪዩርፓይፕ አሶሴሽን፣ ከሩዋንዳው ኪርሄ ቮሊቦል ክለብ፣ ከኬንያው ፕሪዝንስ ኬንያ፣ ከካሜሮኑ ፓድ ቮሊቦል ክለብ እና ከሊቢያው ኢትሃድ ትሪፖሊ ጋር ተደልድሏል። ወላይታ ድቻ የመጀመሪያ ጨዋታውን ዛሬ ከቀኑ 10 ሰዓት ከሊቢያው ኢትሃድ ትሪፖሊ ጋር ያደርጋል። 46ኛው የአፍሪካ የወንዶች የቮሊቦል ክለቦች ሻምፒዮና እስከ ሚያዚያ 22 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል። ሻምፒዮናው በአፍሪካ ቮሊቦል ኮንፌዴሬሽን አስተናጋጅነት ይሚካሄድ ነው። እ.አ.አ በ1980 በተጀመረው የአፍሪካ የወንዶች የቮሊቦል ክለቦች ሻምፒዮና የግብጹ አል አህሊ 16 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዘዋል። የቱኒዚያ ስፋክሲያን ስድስት ጊዜ አሸናፊ ሲሆን የግብጹ ዛማሌክ እና የቱኒዚያው ኤስፔራንስ ደ ቱኒዝ በተመሳሳይ አምስት ጊዜ ዋንጫውን ወስደዋል።
የኢትዮዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ቀን ውሎ
Apr 20, 2025 53
አዲስ አበባ ፤ሚያዚያ 12/2017 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 26ኛ ሳምንት ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። በዕለቱ የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና ከሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ቡና በ39 ነጥብ 2ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሲዳማ ቡና በ32 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቡናማዎቹ ካሸነፉ ከሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን ጋር ያላቸውን ልዩነት ወደ ስድስት ዝቅ ያደርጋሉ። ምሽት 12 ሰዓት ላይ አርባምንጭ ከተማ ከስሑል ሽሬ ይጫወታሉ። አርባምንጭ ከተማ በ34 ነጥብ 8ኛ ደረጃን ይዟል። ስሑል ሽሬ በ17 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በተያያዘ ዜና ትናንት በተደረጉ የ26ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ሀድያ ሆሳዕና ወላይታ ድቻን ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን በተመሳሳይ 3 ለ 1 አሸንፈዋል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ ከስምንት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Apr 19, 2025 78
አዲስ አበባ ፤ሚያዚያ 11/2017 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት ሁለተኛ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቢኒያም ፍቅሩ ሁለት ጎሎችን ሲያስቆጥር አብዱ ሳሚዮ ቀሪዋን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቡልቻ ሹራ ለወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ብቸኛዋን ጎል አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ34 ነጥብ ደረጃውን ከ11ኛ ወደ 9ኛ ከፍ አድርጓል። ከስምንት ጨዋታዎች በኋላም ወደ አሸናፊነት ተመልሷል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ11 ነጥብ የመጨረሻውን 18ኛ ደረጃ ይዟል። ቀን ላይ በተደረገ የ26ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ሀድያ ሆሳዕና ወላይታ ድቻን 3 ለ 1 አሸንፏል።
አስቶንቪላ ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Apr 19, 2025 73
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 12/2017 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት ተጠባቂ ጨዋታ አስቶንቪላ ኒውካስትል ዩናይትድን 4 ለ 1 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማምሻውን በቪላ ፓርክ በተካሄደው ጨዋታ ኦሊ ዋትኪንስ፣ ኢያን ማትሰን፣ አማዱ ኦናና እና የኒውካስትል ዩናይትዱ ተከላካይ ዳን ባርን በራሱ ግብ ላይ ለቡድኑ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ፋቢያን ሻር ለኒውካስትል ዩናይትድ የማስተዛዘኛዋን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ አስቶንቪላ በ57 ነጥብ 6ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመሳተፍ በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። ኒውካስትል ዩናይትድ በ59 ነጥብ 3ኛ ደረጃን ይዟል። በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግን ተሳትፎ ለማግኘት እየተደረገ ያለው ጠንካራ ፉክክር ይበልጥ አጓጊ ሆኗል።
የሊጉ መሪ ባርሴሎና ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Apr 19, 2025 67
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2017 (ኢዜአ):- በስፔን ላሊጋ የ32ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ባርሴሎና ሴልታቪጎን 4 ለ 3 አሸንፏል። ማምሻውን በካምፕኑ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ራፊኒያ በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ምት ሁለት ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ዳኒ ኦልሞ እና ፌራን ቶሬስ ቀሪዎቹን ግቦች ለባርሴሎና አስቆጥረዋል። ለሴልታቪጎ ቦርጃ ኢግሌሲያስ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። ባርሴሎና 3 ለ 1 እየተመራ ጨዋታውን የቀለበሰበት መንገድ አድናቆት አስችሮታል። ውጤቱን ተከትሎ ባርሴሎና በ73 ነጥብ የሊጉን መሪነት አጠናክሯል። ከተከታዩ ሪያል ማድሪድ ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሰባት ከፍ አድርጓል። ሪያል ማድሪድ ከአትሌቲኮ ቢልባኦ ነገ ጨዋታውን ያደርጋል።
ማንችስተር ሲቲ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል
Apr 19, 2025 65
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 12/2017 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ኤቨርተንን 2 ለ 0 አሸንፏል። በጉዲሰን ፓርክ በተካሄደው ጨዋታ ኒኮ ኦለራይሊ እና ማቲዎ ኮቫቺች የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ በ58 ነጥብ ደረጃውን ከ5ኛ ወደ 4ኛ ከፍ አድርጓል። በሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ በሚያደርገው ጉዞ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። ኤቨርተን በ38 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። በሌሎች ጨዋታዎች ብሬንትፎርድ ብራይተንን 4 ለ 2 አሸንፏል። ዌስትሃም ዩናይትድ ከሳውዝሃምፕተን አንድ ለአንድ፣ ክሪስታል ፓላስ ከቦርንማውዝ ዜሮ ለዜሮ በሆነ ውጤት አቻ ተለያይተዋል። ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ በቪላ ፓርክ ስታዲየም አስቶንቪላ ከኒውካስትል ዩናይትድ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
ሀድያ ሆሳዕና ከድል ጋር ታርቋል
Apr 19, 2025 50
አዲስ አበባ ፤ሚያዚያ 11/2017 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት የመጀመሪያ መርሃ ግብር ሀድያ ሆሳዕና ወላይታ ድቻን 3 ለ 1 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብሩክ በየነ፣ በየነ ባንጃ እና ደስታ ዋሚሾ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ዘላለም መንግስቱ ለወላይታ ድቻ ብቸኛዋን ግብ አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ ሀድያ ሆሳዕና በሊጉ ከስድስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል። ቡድኑ በ37 ነጥብ ደረጃውን ከ8ኛ ወደ 4ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ድሉን አግኝቷል። በአንጻሩ በሊጉ 7ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ወላይታ ድቻ በ37 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ 5ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ይጫወታሉ።
የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት መርሃ ግብር
Apr 19, 2025 65
አዲስ አበባ ፤ሚያዚያ 11/2017 (ኢዜአ)፡- የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ በሚደረጉ ጨዋታዎች ይጀመራል። ኤቨርተን ከማንችስተር ሲቲ ከቀኑ 11 ሰዓት፣ አስቶንቪላ ከኒውካስትል ዩናይትድ ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ጨዋታዎቹ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ ጠንካራ ፉክክር እያደረጉ ለሚገኙት ማንችስተር ሲቲ፣ አስቶንቪላ እና ኒውካስትል ዩናይትድ ወሳኝ የሚባሉ ናቸው። በሌሎች መርሃ ግብሮች ብሬንትፎርድ ከብራይተን፣ ዌስትሃም ከሳውዝሃምፕተን እና ክሪስታል ፓላስ ከቦርንማውዝ በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ነገ የሊጉ መሪ ሊቨርፑል ከሌይስተር ሲቲ እንዲሁም ተከታዩ አርሰናል ከኢፕስዊች ታውን ጋር ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 26ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል
Apr 19, 2025 56
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2017(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሃ ግብር የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ወላይታ ድቻ ከሀድያ ሆሳዕና ከቀኑ 9 ሰዓት፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። መርሃ ግብሩ ነገም ቀጥሎ ሲውል ኢትዮጵያ ቡና ከሲዳማ ቡና እንዲሁም አርባምንጭ ከተማ ከስሑል ሽሬ ጋር ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የ26ኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ሚያዚያ 14 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚቆይ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል። ኢትዮጵያ መድን ሊጉን በ48 ነጥብ እየመራ ሲሆን ኢትዮጵያ ቡና በ39 ነጥብ ይከተላል። ባህር ዳር ከተማ እና ወላይታ ድቻ በተመሳሳይ 37 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ሶስተኛ እና አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። ሃዋሳ ከተማ፣ አዳማ ከተማ፣ ስሑል ሽሬ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከ15ኛ እስከ 18ኛ ያለውን ደረጃ በመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛሉ። የአርባምንጭ ከተማው አህመድ ሁሴን እና የሃዋሳ ከተማው ዓሊ ሱሌይማን በተመሳሳይ 10 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመሩ ነው። የኢትዮጵያ ቡናው አንተነህ ተፈራ እና የፋሲል ከነማው ጌታነህ ከበደ በተመሳሳይ 9 ጎሎችን በማስቆጠር ይከተላሉ።
ማንችስተር ዩናይትድ ሊዮንን ድራማዊ በሆነ ሁኔታ በማሸነፍ ወደ ግማሽ ፍጻሜ አለፈ
Apr 18, 2025 122
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 9/2017 (ኢዜአ)፦ በዩሮፓ ሊግ ሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ ሊዮንን 5 ለ 4 አሸንፏል። ማምሻውን በኦልድትራፎርድ ስታዲየም የተደረገው ጨዋታ በልብ አንጠልጣይ ክስተቶች የታጀበ ነበር። ማኑኤል ኡጋርቴ እና ዲዮጎ ዳሎት በመጀመሪያ አጋማሽ ባስቆጠሯቸው ጎሎች ማንችስተር ዩናይትድ 2 ለ 0 መምራት ችሏል:: ኮረንቲን ቶሊሶ እና ኒኮላስ ታግሊያፊኮ ከእረፍት መልስ ከመረብ ላይ ያሳረፏቸው ግቦች ሊዮንን አቻ አድርገዋል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሁለት አቻ በመጠናቀቁ ወደ ጭማሪ 30 ደቂቃ አምርቷል። ራያን ቼርኪ በ105ኛው በጨዋታ እና አሌክሳንደር ላካዜት በ110ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ያስቆጠሯቸው ጎሎች ግብ ሊዮንን 4 ለ 2 መሪ አድርጎ ነበር። ይሁንና ብሩኖ ፈርናንዴዝ በ114ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት፣ ኮቢ ሜይኖ በ120ኛው እና ሀሪ ማጓየር በ121ኛው ደቂቃ ያስቆጠሯቸው ግቦች ለማንችስተር ዩናይትድ ጣፋጭ ድል አስገኝቷል። የሊዮኑ ኮረንቲን ቶሊሶ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ዩናይትድ በድምር ውጤት 7 ለ 6 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ማንችስተር ዩናይትድ በግማሽ ፍጻሜው ከአትሌቲኮ ቢልባኦ ጋር ይጫወታል። አትሌቲኮ ቢልባኦ ሬንጀርስን በደርሶ መልስ ውጤት 2 ለ 0 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። በሌሎች ጨዋታዎች ቶተንሃም ሆትስፐርስ ኢንትራክት ፍራንክፈርትን፣ ቦዶ ግሊምት ላዚዮን በድምር ውጤት በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፈዋል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ቦዶ ግሊምት በግማሽ ፍጻሜው ይገናኛሉ። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በሚያዚያ ወር መጨረሻ ይካሄዳሉ።